የወታደሯ የ3 ቀናት የመቃብር ውስጥ ቆይታ።
የወታደሯ የ3 ቀናት የመቃብር ውስጥ ቆይታ
******************
መ/ወ/ር ተስፋነሽ ጋቢሳ ትባላለች። የመከላከያ ሠራዊቱ ልዩ ኃይል አባል ናት፡፡ ጁንታው በከፈተው ውጊያ ለመፋለም በራያ ግንባር ከክፍሏ አባላት ጋር ተሰልፋ በርካታ ግዳጆችን በድል ተወጥታለች።
ጠላት ለዓመታት ያዋጋኛል ብሎ እንዳዘጋጀው በወታደራዊ ጠበብቶቹ በግንባሩ መሪ ሌ/ጄ ባጫ ደበሌ እና ሌሎች አመራሮች የተመሰከረለት ልዩ ቦታው አዲ ቀይህ የተባለው ቦታ ላይ ለ3 ቀናት በተደረገው ፍልሚያ በጀግንነት እየተዋጋች ሳለ ያልጠበቀችው ሁኔታ ገጠማት።
በዚህ ቦታ ላይ ጠላት ሙሉ ኃይሉን ተጠቅሞ መዋጋት በመጀመሩ እንደ ሌሎች ምሽጎች በቀላሉ መስበር ካለመቻሉም ባሻገር፣ ጠላትን ለመደምሰስ የገባውን የወገን ጦር ለመቁረጥ መልሶ ማጥቃት በማድረጉ ወገን የኃይል ሚዛኑን ለማመጣጠን እና ሌሎች ወታደራዊ ጥበቦችን ለመጠቀም ሲባል ከጠላት ከበባ ሰብረው እንዲወጡ ሲደረግ መ/ወ/ር ተስፋነሽ በጠላት ቀጣና ተቆርጣ ትቀራለች።
ወ/ር ተስፋነሽ ወገን አሸንፎ ሞሽጉን እንደሚሰብር ሙሉ እምነት ስለነበራት፣ የታጠቀችውን ስናይፐር ጨምሮ መሬቱን ቆፍራ ራሷን ጉድጓድ ውስጥ ትቀብራለች። አፈሩን በእጆቿ በላይዋ ላይ በመመለስ ከመሬቱ ጋር በሚገባ ትመሳሰላለች።
በዚህ ሁኔታ ላይ እያለች ብዙ የጁንታው ታጣቂዎች በላይዋ ላይ እየተረማመዱ ከወዲያ ወዲህ ይመላለሱባታል።
መማረክን ከሞት በላይ የምትፈራው እና ድሉን ሳታይ መሞት የማትፈልገው ጀግናዋ መ/ወ/ር ተስፋነሽ ያላት አማራጭ ሁሉንም ችላ ዝም ማለት ብቻ ነበር።
ነገር ግን ጁንታው ከአጠገቧ ላይ ዲሽቃውን ሲጠምደው፣ አንዱ የዲሽቃው መቋሚያ እግር ከተቀበረችበት አቅራቢያ ላይ አረፈ። ዲሽቃውም ቦታውን ሳይለቅ ከአቅራቢያዋ እየተኮሰ 3 ቀናት ተቆጠሩ።
በእነዚህ ቀናት ራሷን እንደ ሙት ያለ ምንም እንቅስቃሴ ትንፋሿን አምቃ ምድር ውስጥ ሳለች ከፍተኛ ውጊያ ከተካሄደ በኋላ ሠራዊቱ ምሽጉን ሰብሮ ድል ማድረጉን የዲሽቃው መቋሚያ እግርም እሷ ካለችበት ጉድጓድ አካባቢ መነሣቱን አወቀች፡፡
ከጥቂት ደቂቃዎች በኋላ ራሷን ከቀበረችበት በማስነሣት አካባቢውን ስትመለከት ጀግኖች ጓዶቿ ጁንታውን አባርረው ቦታውን ሙሉ በሙሉ ተቆጣጥረውታል።
እሷ ብታውቃቸውም እነሱ ግን ሙሉ ሰውነቷ ከአፈር ስለተመሳሰለ አላወቋትም ነበርና 'እጅ ወደ ላይ' የሚል ድምፅ ሰማች።
እሷም እጆቿን አንሥታ 'ወገን ነኝ ' የሚል ድምፅ በደስታ ብዛት ተውጣ አሰማች። እነሱም ወደ ኋላ በመውሰድ ከ3 ቀናት በኋላ እህል እና ውኃ እንድትቀምስ አድርገዋታል።
መ/ወ/ር ተስፋነሽ ጋቢሳ በአሁኑ ወቅት በሙሉ ጤንነት ወደ መደበኛ ተግባሯ ተመልሳ ጁንታውን ለደምሰስ እየተፋለመች ትገኛለች ሲል ከመከላከያ ሠራዊት የፌስ ቡክ ገጽ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።
No comments:
Post a Comment