Shop Amazon

Wednesday, February 19, 2014

የረዳት ፓይለቱ ሀይለመድህን እህት መልዕክት Message from co-pilot Hailemedin's Sister

በመጀመሪያ ይህን ጽሁፍ የምታነቡ ሰዎች በሙሉ የተዝረከረከ ከሆነባችሁ ይቅርታ እጠይቃለሁ። ከትናንት ከሰዐት በኋላ ጀምሮ እስካሁን ኢንተርኔትና ቴለቪዥን ላይ ያለማቋረጥ ተተክየ ስለቆየሁና በጥልቅ ሃዘን ስለተመታሁ አይምሮየ ትክክል ላይሆን ይችላል።
‘የኢትዮጵያ አየር መንገድን ወደ ሮም ይጓዝ የነበረ አውሮፕላን ጠልፎ ጄነቫ ላይ ያሳረፈው ረዳት አብራሪ እጁን ለስዊዝ ስጠ። ምክንያቱም ስዊዘርላንድ ውስጥ ጥገኝነት ለመጠየቅ ነው ብሏል።’ የሚለውን ዜና በርካታ የዜና ማሰራጫዎች ከየፊናቸው አስተያየት ጋር አቅርበውታል። የዜና ማሰራጫዎች ብቻ ሳይሆኑ የተለያዩ ወገኖች ያሻቸውን ብለዋል። የፖለቲካ ድርጅቶች የሰብዐዊ መብት ተሟጋቾችና እንደ አቤ ቶኪቻው ያሉ ቀልደኞች የየራሳቸውን ሃሳብ ለማስተላለፍ ተጠቅመውበታል። በጣም አሳዝኝ ነገር ነው። ሁሉም የየራሱን እምነት ለማስተላለፍ እንጂ እሱስ ምን ሆኖ ይሆን ብሎ አለማሰቡ ልብ ይሰብራል።
ወንድሜ ሃይለመድህን አበራ የሰዎችን ደህንነት አደጋ ላይ ለመጣል አይደለም እንስሳትን ለመጉዳት የሚፈልግ ሰው አይደልም። ደግሞም ያንን የጨነቀውን ያክል ከፈራው ነገር ለመሸሽ ሞከረ እንጂ ማንንም ባለመጉዳቱና ሃሳብ እንኳ እንዳልነበረው ምንም አይነት ማጥቂያ መሳርያ ባለመታጠቁ አሳይቷል። በሁሉም ዘንድ የሚታወቀው ለተቸገሩ በመድረስና ባዛኝነቱ ነው። ካገር ውጪ ሄዶ ለመኖር የሚፈልግ ሰው ቢሆን ለሱ በጣም ቀላል ነገር ነው። ከጥቂት ወራት በፊትንኳ ዩኤስ ኤ ሄዶ ነበር። ከ አስር ቀናት በላይንኳ መቆየት አልፈለገም። ዝም ብሎ ካገር መውጣት ቢፈልግ ከዛ የተሻለ አጋጣሚ አልነበረም። ደግሞም በኑሮ ደረጃ ውጪ ቢኖር ያን ያክል የሚያሻሽለው ነገር አይደለም። ምክንያቱም የገንዘብ ችግር የለበትም። ከራሱም አልፎ ለብዙ ሰዎች የሚተርፍ ገቢ ነበረው።
ከልጅነቱ ጀምሮ ጎበዝ ሳይሆን እጅግ በጣም ጎበዝ ጭንቅላት ያለው ወጣት ነው። አብዛኛዎቹን ክፍሎች ሁለት ሁለት እያለፈ አስራ ሰባት አመት ሳይሞላው ሀይስኩል ሲያጠናቅቅ የ አስራሁለተኛ መልቀቂያ ውጤቱ ሁሉም ኤ ነበር። የጀመረውን የ አርክቴክቸር ትምህርት ትቶ ወደ ፓይለትነት የገባው ለሙያው ካለው ፍቅር የተነሳ ነው። ለኢትዮጵያ አየር መንገድም የተለየ ክብር አለው።
ሃይለመድህን ሁሉንም አስታዋሽ ቤተሰቡን የሚወድና ተጫዋች ሰው ነበር እስከ ቅርብ ጊዜ። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን ለኛ ያለውን ፍቅር ደህነታችንን በማረጋገጥና የሚያስፈልገንን ሁሉ በመታዘዝ ቢገልጽም ከዘመድ ወዳጆቹ ጋር መገናኘትና አቆመ። የወትሮው ጨዋታና ደስተኝነቱ ቀርቶ ብቸኝነትን የሚወድ ዝምተኛ ሆነ። ህይወቱ ደስታ የራቀው መሰለ። በሁኔታው ተደናግጠን ደጋግመን በመጠየቅ ያወቅነው ሊያጠቁት የሚከታተሉት ጠላቶች እንዳሉ እንደሚያምን ነው። ስልኩን እንደጠለፉት ያስባል፤ በላፕቶፑ ካሜራ ሳይቀር ያዩኛል ብሎ ስለሚሰጋ ካሜራውን ሳይሸፍን አይከፍተውም፤ ወጥቶ እስኪገባ ቤቱን ሲበረብሩ የቆዩ ስለሚመስለው ካሜራ ጠምዶ መሄድ ሁሉ ጀምሮ ነበር። ባጠቃላይ በታላቅ የመንፈስ ጭንቀት እየተሰቃየ ነው። የሚያሳዝነው ደግሞ ይህንን ጉዳቱን ለኛ ለቤተሰቡንኳ አብራርቶ አለመናገሩ ነው። ወንድሜ ለሰዎች እርዳታ ለመድረስና የሌሎች አዳኝ ለመሆን የማይታክት ሰውንጂ እንዲህ በሚያንገበግብ ስቃይ ውስጥንኳ ለራሱ አስቦ እርዳታን የሚጠይቅ ሰው አይደለም። ሁኔታውን በደበስባሳው በታወቀበት ጊዜንኳ የሚያስፈልገውን የህክምና በማቅረብ ስላልረዳነው ቤተሰቡ ሁሉ እንደግር ሳት ይከነክነዋል።እሱ ግን እንዲህ ባለ ጥልቅ የመንፈስ ጭንቀት ውስጥንኳ ለኛ አንድም ቀን ሳያስብ ቀርቶ አያውቅም።
ይህን የምታነቡ ወገኖች ሁሉ ዛሬ እኔ ይሄን ከምጽፍ እግዚአብሄር ምስክሬ ነው እሱ ወደነበረበት ጤናና ሁኔታ ተመልሶ እኔ ሞቼ ቢሆን እመርጣለሁ። ውሸት ከሆነ ይህንን በማድረግ የውሸቴን መልስ እንዲያሳየኝ አምላኬን እለምነዋለሁ። በኛ አገር መስሪያ ቤቶች የሰዎችን እውቀት ብቃትና ቁመና ሳይቀር ሲመዝኑ የዐይምሮ ጤንነት ሁኔታን አለመከታተላቸው እጅግ የሚያሳዝን ነገር ነው።
ወንድሜ ትናንት አውሮፕላኑ ውስጥ ከመግባቱ በፊት ምን አጋጥሞት ይሆን እነዛ የሚላቸው ሰዎች ሲመለስ ጠብቀው እንደሚገሉት ዝተውበት ያንን ፈርቶ ይሆን ወይም ፓይለቱ ከጠላቶቹ ጋር በመተባበር ሊይጠቃው እንደሚችል ብማመን ሰግቶ ይሆን ሲወጣ ራሱን ለመከላከል በሩን የዘጋው ከሁለቱ አንዱ ወይም ሁለቱም እንደሆነ አምናለሁ። አስቡት በዛች ቅጽበት አለሙን በሙሉ ሊያናጋ የሚችል ምንም አይነት ራሱን ሊከላከልበት የሚችል መሳርያ ሳይዝ ይህንን ድርጊት የሚያስፈጽም ምን ነገር ሊኖር ይችላል ስዊዘርላንድ ገነት አይደለችም። የዐይምሮ ህመም ሰለባ የሆኑ ሰዎችን ለዚያውም በማንም ላይ ምንም ጉዳት ባልፈጸሙበትና ሊፈጽሙም ባላሰቡበት ሁኔታ ወደስር ቤት እንዲወረወሩ ህግ የሚፈቅድ አይመስለኝም። ሃይለመድህን ለህይወቱ ሰግቶ ነበር። የሰው ልጅ ሊቋቋመው በማይችል የመንፈስ ጭንቀት ገሃዱና ሃሳባዊው አለም በተዘበራረቀበት የስቃይ አለም ውስጥ ብቻውን ሲሰቃይ ነው የቆየው። በተስተካከለ የዐይምሮ ጤንነት ላይ የሚገኝ ሰው ላይገባው ይችላል። እኔ ግን የሱን ግማሽ ባያክልም የተወሰነ ይህንን መሰል ችግር ስላለብኝ ህመሙን አውቀዋለሁ። ሁሌም በሳት እየተጠበሱ መኖር ማለት ነው
ወገኖች መልዕክቴን አንብባችሁ በምትችሉት ሁሉ ረዳት ፓይለት ሃይለመድህን አበራ ፍትህ አግኝቶ ወደ ነበረበት እንዲመለስ በመጣር እንድትተባበሩን መላ ቤተሰቡ በምታምኑት ሁሉ እንለምናችኋለን! እኛም የሚያስፈልገውን የህክምና እርዳታ አግኝቶ ወደ ቀድሞው ጤናው ከተመለሰ በኋላ ለዚች አገር ባለው አቅም ሁሉ እንዲያገለግል በማድረግ እንክሳለን!
እባካችሁ ይህን መልእክት በማስተላለፍ ተባበሩን!

No comments:

Post a Comment