Shop Amazon

Monday, July 27, 2015

በመርካቶ ለአንድ ካሬ ሜትር ቦታ ከ355 ሺሕ ብር በላይ ቀረበ





በመርካቶ ለአንድ ካሬ ሜትር ቦታ ከ355 ሺሕ ብር በላይ ቀረበ
-በክብረ ወሰን ከተመዘገበው በ50 ሺሕ ብር ብልጫ አለው
ባለፈው ዓርብ ሐምሌ 17 ቀን 2007 ዓ.ም. በተከፈተው 15ኛው የሊዝ ጨረታ፣ በአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ መርካቶ ይርጋ ኃይሌ የገበያ ማዕከል ጀርባ የቀረበው 222 ካሬ ሜትር በካሬ ሜትር 355,550 ብር የመጫረቻ ዋጋ ቀረበለት፡፡ ይህ አዲስ የሊዝ ክብረ ወሰን ሆኖ ተመዝግቧል፡፡




ለዚህ ቦታ ይህንን የመጫረቻ ዋጋ ያቀረበው ስኬት ኢንተርናሽናል የተባለ ድርጅት ሲሆን፣ በመርካቶ በ11ኛው የሊዝ ጨረታ ተይዞ ከነበረው 305 ሺሕ ብር የሊዝ ዋጋ በ50,550 ብር ብልጫ አለው፡፡
ለዚህ ቦታ በሁለተኛ ደረጃ የቀረበው የመጫረቻ ዋጋ በካሬ ሜትር 355 ሺሕ ብር ሲሆን፣ ይህ ዋጋ ቀደም ሲል በክብረ ወሰን ደረጃ ተይዞ ከነበረው መጫረቻ ዋጋ በ45,550 ብር ብልጫ ያለው ነው፡፡ ይህ ኩባንያ ለጊዜው ስሙን ማወቅ አልተቻለም፡፡
መርካቶ አካባቢ ከፍተኛ ገንዘብ የቀረበለት ቦታ በ11ኛው ሊዝ ጨረታ የወቅቱ ሪከርድ የተመዘገበበት 449 ካሬ ሜትር ቦታ ነው፡፡ ይህ ቦታ ዝዋይ ኢንተርናሽናል ትሬዲንግ 305 ሺሕ ብር በካሬ ሜትር ያቀረበለት ቢሆንም፣ ውል ሳይፈጸም መቅረቱን መዘገባችን ይታወሳል፡፡
ይህ ቦታ በ15ኛው ሊዝ ጨረታ በድጋሚ የቀረበ ሲሆን፣ በአንድ ካሬ ሜትር 286,500 ብር ተሰጥቶታል፡፡ ይህንን መጫረቻ ዋጋ ያቀረበው ኤቲኤ ኮንስትራክሽን ኩባንያ ሲሆን፣ ኤቲኤ ያቀረበው ዋጋ ቀድሞ ከነበረው በ18,500 ብር ያነሰ ነው፡፡
ለዚህ ቦታ በሁለተኛ ደረጃ የቀረበው ገንዘብ 282 ሺሕ ብር ነው፡፡ ይህንን ዋጋ ያቀረበው የርፋድ ኩባንያ ነው፡፡

የሊዝ ባለሙያዎች ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ለዚህ ቦታ ቀደም ሲል የቀረበው ዋጋ ከፍተኛ መሆኑ በኅብረተሰቡ ዘንድ መነጋገሪያ አጀንዳ የነበረ በመሆኑ፣ ሌሎች ተጫራቾች በድጋሚ ለመወዳደር ድፍረት አይኖራቸውም በማለት ዋጋው ዝቅ ብሎ ቀርቦ ሊሆን ይችላል፡፡ ነገር ግን ቦታው ከዚህ ዋጋ በላይ ሊያወጣ እንደሚችል ባለሙያዎቹ መከራከሪያቸውን ያቀርባሉ፡፡
መርካቶ አካባቢ ከሰባተኛ ወደ አማኑኤል ሆስፒታል በሚወስደው መንገድ ወደ ውስጥ ገባ ብለው የሚገኙት ሁለት ባለ 150 ካሬ ሜትር ቦታዎች 14,000 እና 12,000 ብር በካሬ ሜትር ቀርቦላቸዋል፡፡
ሌላኛው የዙሩ ከፍተኛ መጫረቻ ዋጋ የቀረበው በኮልፌ ቀራኒዮ ክፍለ ከተማ ቤተል ሆስፒታል አካባቢ ነው፡፡ በዚህ አካባቢ ሁለት ቦታዎች የቀረቡ ሲሆን፣ 159 ካሬ ሜትር ስፋት ላለው ቦታ ጋቢ አሰፋ የተባሉ ባለሀብት ደግሞ ለሁለተኛው ቦታ በካሬ ሜትር 47,512 ብር አቅርበዋል፡፡ ዓለማየሁ ተፈራ የተባሉ ባለሀብት በካሬ ሜትር 32,189 ብር አቅርበዋል፡፡
ስማቸውን መግለጽ ያልፈለጉ የአዲስ አበባ ከተማ ከፍተኛ የመሬት ባለሙያ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ መርካቶ አካባቢ ለወጣው የሊዝ ጨረታ የቀረበው መጫረቻ ዋጋ ከፍተኛ ቢሆንም፣ ከቦታው አንፃር አዋጭ ነው፡፡ ባለሙያው ምክንያታቸውን ሲያስረዱ፣ መርካቶ ላይ ለአንድ መደብ በቀን ከ3,500 ብር እስከ 4,000 ብር ድረስ ኪራይ ይከፈላል፡፡ በሕንፃ ደረጃ ደግሞ ከ12 ካሬ ሜትር ላነሰ ቦታ በወር ከ30,000 እስከ 50,000 ብር ድረስ ይከራያል፡፡
ከፍታ ያለው የገበያ ማዕከል በመገንባት ከፍተኛ ገንዘብ ማግኘት ስለሚያስችል፣ ተጫራቾች የሚያቀርቡት ገንዘብ አዋጭ እንደሚሆንላቸው ይታመናል በማለት ገልጸዋል፡፡ 15ኛው የሊዝ ጨረታ ውጤት ካለፈው ረቡዕ ጀምሮ ይፋ መሆን ጀምሯል፡፡
Reporter: 26 July 2015 ተጻፈ በ ውድነህ ዘነበ

No comments:

Post a Comment