*************************
በአማራ ክልል የሚገኙ 23 ከተሞች በከተማ አስተዳደርነት እንዲመሩ መወሰኑ ተገልጿል፡፡
በከተሞች የአደረጃጀት ፈርጅ መወሰኛና ማቋቋሚያ ደንብ ቁጥር 65/2001 መሰረት መስፈርት አሟልተው የተገኙ 23 ከተሞች ከፈርጅ ሶስት ወደ ፈርጅ ሁለት የደረጃ ሽግግር ማለትም በከተማ አስተዳደርነት ለመመራት በክልሉ ከተማ ልማትና ቤቶች ኮንስትራክሽን ቢሮ አጥንቶ ያቀረበውን የውሳኔ ሀሳብ ተቀብሎ ም/ቤቱ አጽድቋል፡፡
ምክር ቤቱ በጉዳዩ ላይ በስፋት መክሮ የከተሞችን የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች ከመፍታትና ወደ ፊት ያላቸውን የመልማት ዕድል የተጠቀሱ ከተሞችን የደረጃ ሽግግር አጽድቋል፡፡
በዚህም መሰረት ከደቡብ ጎንደር ዞን ወገዳ፣ሀሙሲት እና እብናት፣ከአዊ ብሄረሰብ ዞን አዲስ ቅዳም፣አገው ግምጃ ቤት፣ፈንድቃ፣ከምስራቅ ጐጃም ዞን ደብረ ወርቅ፣ሉማሜ አማኑኤል እና ግንደ ወይን፣ከምዕራብ ጐጃም ዞን ሽንዲ፣ጅጋ ከተሞች ይገኙበታል፡፡
ከደቡብ ወሎ ዞን ከለላ፣ቱሉአውሊያ፣ሀርቡ፣አቅስታ፣ደጎል፣ ከሰሜን ሽዋ ዞን ደብርሲና፣ሞላሌ፣አንዋሪ፣ከሰሜን ወሎ ዞን ጋሸና እንዲሁም ከማዕከላዊ ጎንደር ዞን ደግሞ ቆላ ድባ እና ሻውራ ከተሞች መስፈርቱን ያሟሉ ሆነው በመገኘታቸው በከተማ አስተዳድር እንዲመሩ ተወስኗል፡፡
በመሆኑም ከ2013 ዓ.ም ጀምሮ የተጠቀሱ ከተሞች ከፈርጅ ሶስት ወደ ፈርጅ ሁለት የደረጃ ሽግግር በማድረግ የከተማ አስተዳደርነት ዕውቅና እንዲያገኙ የክልሉ መስተዳድር ምክር ቤት ወስኗል፡፡
ተግባራዊነቱን በተመለከተም ክልሉ ካለበት ነባራዊ ሁኔታ አንፃር የበጀት እጥረት ያገጠመ በመሆኑ የደረጃ ሽግግር የተፈቀደላቸው 23ቱ ከተሞች ከክልል የስራ ማስኬጃም ይሁን ሌላ በጀት የማይመደብ መሆኑን አውቀው በራሳቸው በጀት ቁጠባን መሰረት በማድረግ ወደ ስራ መግባት እንዳለባቸው ማስታወቁን ከአማራ ክልል ፕሬዝዳንት ጽ/ቤት ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡
No comments:
Post a Comment